ወጣቶች ለሀገር ግንባታና ለዘላቂ ሰላም በንቃት ሊሳተፉ ይገባል - አቶ አደም ፋራህ
ወጣቶች የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባትና ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል አሉ በም/ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፡፡
የሰላም ሚኒስቴር ከወጣቶች አደረጃጀት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ‘ወጣቶች ለሰላም’ ሀገራዊ ንቅናቄ ማጠቃለያ መርሐ ግብር ''ሀገሬን እገነባለሁ ሃላፊነቴንም እወጣለሁ'' በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ነው።
በመርሐ ግብሩ ላይ አቶ አደም ፋራህ፣ የሰላም ሚኒስትር መሃመድ ኢድሪስ፣ ሚኒስትር ዴዔታዎች፣ በብልጽግና ፖርቲ የወጣቶች ክንፍ ፕሬዚዳንት አክሊሉ ታደሰ እና ከመላ ሀገሪቱ የተወጣጡ ወጣቶች ተሳትፈዋል።
አቶ አደም ፋራህ በመድረኩ ባደረጉት ንገግር፥ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህ ረገድ ወጣቶች የተሻለችና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።
ወጣትነት ሰላምን፣ ልማትን፣ ዕድገትንና ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ቁልፍ መሳሪያ እንደሆነም አውስተዋል።
ወጣቶች በሀገር ግንባታ የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ የተለያዩ አማራጮችን በማዘጋጀት እየተሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል።
ወጣቶች የሰላምን ጽንስ ሃሳብና ዋጋ በሚገባ በመረዳት በዘላቂ ሰላም ግንባታ ላይ በንቃት ሊሳተፉ ይገባል ነው ያሉት።
አቶ መሃመድ ኢድሪስ በበኩላቸው፥ ወጣቶች ዘላቂ ሰላምን ለመጠበቅ የበኩላቸውን በመወጣት ሀገርን ለትውልድ ለማስተላለፍ ሊሰሩ ይገባል ብለዋል።
የትውልድ ቅብብሎሽ አደራን በሚገባ ለማስተላለፍ የወጣቱ ሚና ከፍተኛ በመሆኑ በቁርጠኝነት ሊሰራ ይገባል ነው ያሉት።
ወጣቶች የሀገር ትልቅ ገጸበረከቶች ናቸው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ባላቸው እምቅ ሃይልም ለሀገር ግንባታ አይተኬ ሚና ይጫወታሉ ሲሉ አንስተዋል።
ወጣቶች የሚያጋጥሙ ተግዳሮቾችን በጥበብ ማለፍ እንዳለባቸው ጠቅሰው፥ በተለይም በማህበራዊ ትስስር ገጾች ከሚሰራጩ ሐሰተኛ፣ የጥላቻና አፍራሽ መልዕክቶች ራሳቸውን ሊጠብቁ ይገባል ብለዋል።
ወጣቶች በሁሉም ልማታዊ ሥራዎች በሚገባ ተሳትፈው ለተጀመረው ሀገራዊ ግንባታ ሚናቸውን እንዲወጡ በትኩረት እየተሰራ ነው ያሉት ደግሞ አቶ አክሊሉ ታደሰ ናቸው።
ወጣቶች የሕዝቦችን አንድነት የሚሸረሽሩ ሀሰተኛ እና የጥላቻ መልዕክቶችን ለመመከት የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡም ጠይቀዋል።