መጋቢት 24 የዜጋ ክብርና ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ አዲስ ምዕራፍ
መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም የለውጡ መንግሥት ሀገራዊ ኃላፊነትን ሲረከብ ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲን በመከተል የዜጋ ክብር የጀመረበት አዲስ ምዕራፍ ነበር፡፡ የለውጡ መንግስት ዲያስፖራውን እንደ ባዕድ ወይም እንደ ስጋት የመመልከት ጠባብ አስተሳሰብ በመስበር፣ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በዓለም አቀፍ መድረክ የአገሩን ክብር ተካፋይ እንዲሆን አድርጓል፡፡
ለውጡ ሲጀምር መንግሥት የዜጎችን ደህንነትና መብት ማስከበርን ቀዳሚ የዲፕሎማሲ አጀንዳ አድርጎ ነው የጀመረው። መንግስትም ያሳየው ቁርጠኝነት ከቃላት ባለፈ በተግባር የተፈተነ ነበር፡፡ በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ወደ ተለያዩ አገራት ባደደርጓቸው ጉብኝቶች ሁሉ፣ በእስር ላይ የሚገኙ ወገኖችን በገዛ አውሮፕላናቸው ጭምር ይዘው በመመለስ ያሳዩት አርአያነት፣ መንግሥት ለዜጎቹ የሚሰጠው ዋጋ ምን ያህል ከፍ ያለ መሆኑን ለመላው ዓለም ያበሰረ ታላቅ መልእክት ሆኗል፡፡
በመካከለኛው ምስራቅና በሌሎች አገራት የሚገኙ ዜጎች መብታቸው እንዲከበር ከሀገራቱ ጋር የተደረጉ የሁለትዮሽ ስምምነቶች፣ ዜጎች በሰው አገር የበይ ተመልካች ሳይሆኑ በሕግ የተጠበቀ ክብር እንዲኖራቸው አስችሏል፡፡ በተለይም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖችን ወደ አገራቸው በመመለስ ረገድ የተከናወነው የተቀናጀ ሥራ፣ የመንግሥትን የመፈጸም አቅም በተግባር አሳይቷል፡፡
ዲያስፖራው እንደ ቤተሰብ መቆጠሩ በመንግሥትና በዜጎች መካከል የነበረውን የጥርጣሬ ግንብን አፍርሶታል፡፡ በዚህም ምክንያት ዜጎች በአገራዊ ጉዳዮችና በዲፕሎማሲያዊ ተጽዕኖ ፈጣሪነት ረገድ ከኢትዮጵያ እውነት ጎን በጽናት እንዲቆሙ ትልቅ መነሳሳትን ፈጥሯል፡፡
በአጠቃላይ ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲው ኢትዮጵያን ለዜጎቿ የምትቆም አገር መሆኗን ከማረጋገጡም በላይ፣ የውጭ ግንኙነታችንን ከደረቅ ቢሮክራሲ ወደ ሕያውና ሰው ተኮር ግንኙነት በመቀየር አገራዊ ኩራታችንን ከፍ አድርጎታል፡፡
#prosperity