ሳምንታዊ መልእክት
ሳምንታዊ መልዕክት
ኢትዮጵያ ታከናውናለች፡ ማከናወኗም ለዓለም ታበስራለች!
ሀገራችን ለበርካታ ዓመታት ስለ ግዙፍ አቅሟ ስትናገር ቆይታለች፤ ዛሬ ግን ይህን አቅም ወደ ተጨባጭ ውጤት የመቀየር አቅሟን በተግባር እያሳየች ነው። ዛሬ ኢትዮጵያ የምትመዘነው ባለፈው ብቻ ሳይሆን እየሰራችው ባለው አዲስ ታሪክ ነው። የኢትዮጵያ የቅርብ ዓመታት የለውጥ ጉዞ በአጋጣሚ የተከሰተ ሳይሆን በጥንቃቄ የተሰላ እና በብልፅግና ፓርቲ የመደመር እሳቤ የተገለጠ የረዥም ጊዜ የመዋቅር ማሻሻያ ውጤት ነው። ብልፅግና ፓርቲ የኢትዮጵያን የክፍለ ዘመናት የኋላ ታሪክ በጥልቀት በመመርመር ያለፉት ሥርዓቶች ሳያሳኳቸው የቀሩት የቤት ሥራዎችን በመለየት ሀገሪቱን ወደ አዲስ የልማት ምዕራፍ በማሸጋገር ላይ ይገኛል። ከጥቂት ቀናት በፊት “ኢትዮጵያ ታከናውናለች/Ethiopia Delivers” በሚል መሪ ቃል የተካሄደው ልዩ ሀገራዊና ዓለምአቀፋዊ ጉባኤ የዚህ ምዕራፍ ማሳያ ነው፡፡ ጉባኤው ኢትዮጵያ ምኞቷን ብቻ ሳይሆን ያከናወነቻቸውን ስኬቶች ለዓለም ማብሰር መጀመርዋን ያረጋገጠ መድረክ ነው።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፣ ከፍተኛ የፓርቲና የመንግሥት አመራር፣ ዲፕሎማቶች፣ ዓለምአቀፍ ባለሀብቶች፣ የልማት አጋሮች እና የግሉ ዘርፍ ተወካዮች በተገኙበት የተካሄደው ይህ ጉባኤ ኢትዮጵያ በአምስቱ የኢኮኖሚ ምሰሶዎች ማለትም በግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም እና ኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ እየተካሄደ ያለውን ሁለገብ ለውጥ አሳይቷል። ከሁሉም በላይ ትግበራን እና ሊለኩ የሚችሉ ውጤቶችን በሀገራዊ ልማት እምብርት ላይ ያስቀመጠ አዲስ ለውጥ መፈጠሩን ተመላክቷል።
መድረኩ ብልፅግና ፓርቲ የተቀበለዉን የህዝብ አደራ በሥራ ለመተርጎም የሚያደርገውን የተቀናጀ ጥረት እና የለውጥ ፍጥነት የሚያንጸባርቅ ነው። ብልፅግና ፓርቲ የመንግሥት ቅቡልነትን የሚገኘው ከፖለቲካ ፍልስፍናና ራዕይ ብቻ ሳይሆን ከአፈጻጸም እንደሆነ በጽኑ ያምናል፤ ቃል ኪዳን ብቻ ማህበረሰብን አይቀይርም፣ ፖሊሲዎች ብቻ የዜጎች ህይወትን አይለውጡም። የሀገር ለውጥ የሚለካው ፓርቲና መንግስት ማሻሻያዎችን በመተግበር፣ የህዝብ ጥቅምን በማስቀደም፣ ተቋማትን በማጠናከር እና የዜጎችን የዕለት ተዕለት ኑሮ በማሻሻል ነው። ይህ የአፈጻጸም መርህ በብልፅግና ፓርቲ የሚመራው የኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ዋና መገለጫ ሆኗል። ከዚህ በመነሳት በቀደሙ ሥርዓታት የነበሩ የልማት ዉሱንነቶችንና የፖሊሲ መዛነፎችን በመማሪያነትና በቁጭት አጀንዳነት በመውሰድ የኢትዮጵያን ልማት ወደ ስልታዊ ለውጥ ተሸጋግሯል፡፡
ለምሳሌ ኢትዮጵያ ባለፉት ስምንት ዓመታት ያካሄደችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ደም ስር እንዳዲስ ያነቃቃ ነው። ኢኮኖሚው ገበያ መር እና በታቀደ መልኩ ለዓለምአቀፍ ውድድር ክፍት እንዲሆን መደረጉ ለኢኮኖሚው መነቃቃት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል። የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠር የተወሰዱት የገንዘብ ፖሊሲ እርምጃዎች ኢኮኖሚው በእውነተኛ የለውጥ ሀዲድ እንዲጓዝ አስችሎታል፡፡ የግብርናው ዘርፍ መዘመን እና የኢንዱስትሪው ድርሻ ከማንኛውም ጊዜ በላይ ማደጉ ኢትዮጵያ ከአግሮ-ኢኮኖሚ ወደ ኢንደስትሪላይዜሽን እየተሸጋገረች መሆኑን በግልጽ አሳይቷል፡፡ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ለባንክ ብድርና ፋይናንስ አገልግሎት ተደራሽ መሆናቸው እና የግል ዘርፉ ትልቁ የሀገሪቱን ብድር ተጠቃሚ እንዲሆን መደረጉ ማክሮ ኢኮኖሚው በውጤታማነት ታጅቦ በዘላቂ መንገድ እየተጓዘ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡
ስለሆነም “ኢትዮጵያ ታከናውናለች” የሚለው አገላለጽ በስራ እና በአፈጻጸም ላይ የተመሰረተ የብልፅግና ፓርቲ ቃልኪዳን ነው። በዚህ መንገድ የመጣው የኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ለህዝብ፣ ለውስጥና ለውጭ ባለሀብቶች እና ለዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ የሚሰጠው መልእክት ግልጽ ነው፡፡ ኢትዮጵያ አሁን የተረጋጋች፣ ዲሲፕሊን ባለው አመራር የምትመራ እና ለዘላቂና ሁለንተናዊ ብልፅግና የተዘጋጀች ሀገር ነች። ዜጎቿም በታሪክ አውድ ውስጥ የሚጓዙ፣ በመደመር መርህ የሚመሩ እና ውጤትን እንደ ዋና መለኪያ የሚጠቀሙ ናቸው፡፡ ይህ የመደመር ትውልድ ኢትዮጵያን በጠንካራ መሠረት ላይ ለመገንባት ቆርጦ ተነስቷል፤ የለውጥና የማከናወን ጉዟችን ቀጥሏል፤ ስኬታችንም ለዓለም መበሰር ጀምሯል፡፡ ስለሆነም ሁሉም ዜጋ በዚህ አስደናቂ የለውጥ ጉዞ ላይ አሻራዉን እያሳረፈ እንዲቀጥል እና የለውጡን ትሩፋት ተቋዳሽ እንዲሆን ብልፅግና ፓርቲ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
ኢትዮጵያ ታከናውናለች፡ ማከናወኗም ለዓለም ታበስራለች!
ብልፅግና ፓርቲ
ሰኔ 22፤ 2018 ዓ/ም