ይህ ዘመን በታሪካችን ውስጥ በጉልህ የሚነሳ ነው
ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና በፌዴሬሽን ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት ላይ ይህ ዘመን በታሪካችን ውስጥ በጉልህ የሚነሳ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
እኛ ኢትዮጵያውያን ለበርካታ ዘመናት ስንቆጭባቸው የነበሩትን ታላላቅ ፕሮጀክቶች ያስመረቅንበት ልዩ ዓመት አሳልፈናል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ የትውልዱ ቁጭት የነበረውን የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ አጠናቀን ታሪክ ሰርተናል ብለዋል።
በመስከረም ወር መጀመሪያ የኢትዮጵያ የከርሰ ምድር ሀብት የብስራት ጅማሮ የሆነውን የተፈጥሮ ጋዝ ያወጣንበት እና የተፈጥሮ ሀብታችንን ተጠቅመን ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን የጀመርንበት በመሆኑ፣ ይህ ዘመን በጉልህ የሚነሳ እና አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ሲሉ ተናግረዋል።
በኢኮኖሚው ላይ መንግሥት ረጅም ጥናት አካሂዶ የጀመረው የማይክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ፤ ኢኮኖሚው ላይ ያመጣው ለውጥ በግልጽ የታየበት እንደነበር አንስተዋል፡፡
በዚህም መንግሥት ኢኮኖሚውን ከነበረበት የዕዳ ጫና በማላቀቅ ወደ ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት ለማሸጋገር የሚያስችል ወሳኝ ሂደት ላይ ይገኛል ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።
በኢኮኖሚ ላይ በተሰሩ ተከታታይነት ባላቸው ሥራዎች፣ የወጪ ንግድ እና የውጭ ምንዛሬ ክምችት ጨምሯል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በግብርና እና በማዕድን ዘርፎች ላይ በተሠራው ውጤታማ ሥራ ፍሬውን ማየት ጀምረናል ሲሉም አክለዋል