ብልፅግናን እውን ለማድረግ ሕዝቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
የዜጎችን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል እና ብልፅግናን እውን ለማድረግ ሕዝቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ አሉ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች፡፡
የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ እየተሰጠ ነው፡፡
"በመደመር መንግሥት ዕይታ የዘርፎች እመርታ" በሚል መሪ ሐሳብ በተሰጠው ስልጠና ላይ ከ2 ሺህ በላይ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
ከስልጠናው በተጓዳኝ ሰልጣኞቹ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።
በጉብኝቱ የተሳተፋ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች፥ የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳኩ ውጤቶችን መመልከታቸውን ገልፀዋል፡፡
በኢትዮጵያ በገጠርም በከተማም ለውጥ የሚያመጡ ሥራዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ በስልጠናው እነዚህን ውጤቶች በላቀ ደረጃ ማስቀጠል በሚቻልበት አቅጣጫዎች ላይ ተግባብተናል ነው ያሉት።
ሕዝቡን በልማት ተጠቃሚ በማድረግ የኑሮ ሁኔታው እንዲሻሻል በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል።
እየተመዘገቡ ያሉ ድሎች የፓርቲው ፖሊሲዎችና አቅጣጫዎች ውጤት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ስልጠናውም ተሞክሮ ልውውጥ በማድረግ እና የጋራ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ዕድል የሰጠ መሆኑንም አንስተዋል።
ብልፅግናን በላቀ ደረጃ ለማረጋገጥ ሕዝቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልጸው፤ ጉብኝቱ የኢትዮጵያ ብልፅግና አይቀሬነት መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡
የሚገጥሙ ፈተናዎችን በጋራ በማለፍ የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስኬታማ ተግባራትን ለማከናወን በትጋት መረባረብ ይገባል ብለዋል።