ፕሬዝዳት ሳህለወርቅ ዘውዴ ሦስተኛውን ዙር የ8100 A የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የገቢ ማሰባሰቢያ መርኃ ግብር በይፋ አስጀምረዋል።
የገቢ ማሰባሰቢያ መርኃ ግብሩ ለስድሰት ወር የሚቆይ ሲሆን የመጀመሪያው እጣ የ2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ተሽከርካሪ የሚያሸልም ነው ተብሏል።
መርኃ ግብሩ በሂደት ሌሎችም ሽልማት ያሉት ሲሆን ለሦስት ወር የሚቆይ የጥያቄና መልስ ውድድርም ይካሄዳል።
ፕሬዝዳት ሳህለወርቅ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ ኅብረተሰቡ ግድቡ ከተጀመረ ጀምሮ በተለያዩ ዓይነት ከፍተኛ ድጋፍ አድርጓል እያደረገም ይገኛል ብለዋል።
ግድቡ የህዝቦችን አንድነትና የጋራ ተስፋ የሚያንጸባርቅ የጋራ ሃብት መሆኑን የጠቀሱት ፕሬዝዳንቷ ድጋፉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ኃብቷን የመጠቀም መብቷን ተንተርሳ የአባይ ውኃን ትጠቀማለች፤ ይህም ሕግን ተመስርቶ ነው ብለዋል።
ይህም ዓለም አቀፍ የዘርፉን ሥምምነት ከግምት በማስገባት የሚካሄድና ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው መሆኑንም ተናግረዋል።
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ለግድቡ ግንባታ እስካሁን ከኅብረተሰቡ 18 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ ተችሏል።
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አሁናዊ አፈፃፀምም ከ70 በመቶ በላይ መድረሱ ይታወቃል።