ብልጽግና ፓርቲ የአገራችንን ፖለቲካዊ ችግሮች የሚያይበት የዕይታ ማዕቀፍ በጥቅሉ የነበረውን በማስጠበቅና አዲስ መንገድ በመምራት እኩል ሚዛን የሚጠብቅ ነው፡፡
በዚህም ምክንያት ከወግ አጥባቂ ዝንባሌዎችም ሆነ አፍርሰው ከሚገነቡ አስተሳሰቦች ይልቅ መካከለኛውን መንገድ ተመራጭ ያደርጋል፡፡
በሀገራችን የቀኝ እና የግራ አሰላለፍ በመሰረቱ ከመደባዊ ውግንና ዝንባሌ ባሻገር አጠቃላይ አገረ መንግስቱ ዙሪያ ባሉ ዕይታዎች ላይ የሚያጠነጥን መሆኑን በመረዳት እነዚህን አመለካከቶች የሚያቀራርብ የመሐል አሰላለፍን ይከተላል፡፡
ሆኖም የመሐል አሰላለፉ ነገሮችን ቋሚ አድርጎ ከመመልከት ይልቅ ነባራዊ እውነታን እያነበበና በጥናት ላይ እየተመሰረተ የሚቀጥል ፕራግማቲክ አሰላለፍን የሚከተል ፓርቲ ነው፡፡
በሂደቱም መርህን ተከትሎ ጉዞን የመፈተሸ አካሄድ ላይ ትኩረት ያደርጋል፡፡ሁሉንም ኢትዮጵያዊያን የሚያሰባስብና የፓርቲው ማህበራዊ መሰረት ማድረግ የሚያስችል አካታች ፖለቲካዊ ጉዞን ተመራጭ ያደርጋል፡፡ሀገራችን ለሁላችንም ትበቃለች የሚል ጽኑ ሃሳብ በመያዝና የዕጦት አስተሳሰብን በመሻገር ለሁሉም ዜጎች የምትሆንና ሁሉም በኩራት እና በምቾት የሚኖርባት ኢትዮጵያን ለመፍጠር ትግል ያደርጋል፡፡