ኢትዮጵያ አዲሱን የልማት ዘመቻ በዛሬው እለት የፓርቲያችን ፕሬዚዳንት ዶክተር ዐቢይ አህመድ አማካኝነት ይፋ አድርጋለች
ዘመቻው የሌማት ትሩፋት በሚል መሪ ቃል በዛሬው እለት የተጀመረ ሲሆን በስንዴ ምርት እያስመዘገብን ለሚገኘው የምግብ ዋስትናችንን የማረጋገጥ ጥረት ተጨማሪ አቅም ሊሆን የሚችል ዘመቻ ነው፡፡
በስንዴ ምርት የምናገኘውን ውጤት በተትረፈረፈ መልኩ በእንስሳት ተዋእፆ ማጀብ እንድንችል ይህ ዘመቻ ከፍተኛ አቅም ይፈጥርልናል፡፡
በዚህም በእንቁላል፤በስጋ፤በወተት እና በማር ምርቶች ላይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት የምንንቀሳቀስ ይሆናል፡፡
ዘመናዊ የሆኑ የግብርና ዘዴዎችን በመጠቀም በውስን ቦታ ውስጥ ምርታማነታችንን ማሳደግ የሚቻልበት አቅም ለመፍጠር ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ የሚሰራበት ሲሆን አዳዲስ ሀገር በቀል የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በማበልፀግ ዘመቻው ግቡን እንዲመታ አቅም የሚፈጠር ይሆናል፡፡
የንብ ቀፎዎቻችን በማር የተሞሉ ሆነው ከምግብ አልፎ ለመድሀኒት ምርምር፤ለጤና አገልግሎት እንዲሁም ለኤክስፖርት ምንጭ ሆነው ለኢኮኖሚያችን እድገት አስተዋፆ እንዲያደርጉ ይፈለጋል፤የዶሮ እርባታችን ስጋቸው የፋፋ የሚሰጡት አመታዊ የእንቁላል ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ያደገ ለምግብ ዋስትናችን መረጋገጥ አስተዋፆ የሚያደርግ ሊሆን ይገባዋል፤የቀንድ ከብቶቻችን በተመሳሳይ ስጋን፤ወተትን እንዲሁም የቆዳ እና ሌጦ ግብአታችንን የማሳደግ አቅም ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከሁሉም የሚገኘው ውጤትም እሴት ተጨምሮበት ወደ ገበያ መቅረብ እንዲችል የቴክኖሎጂ፤የዘመናዊ አሰራር ስርአት እንዲሁም አምራች እና ተጠቃሚን የሚያገናኝ የእንስሳት እርባታ በሀገራችን የቅንጦት ምልክት ተደርጎ የሚወሰደውን አስተሳሰብ መቀየር የሚያስችል ውጤት መፍጠር በዚህ ዘመቻ ይጠበቃል፡፡
በመዝራት ያመጣነውን ለውጥ በማርባት መድገም አለብን፡፡ ግሬራዎች በወተት ሊሞሉ፣ ቅቤ እና ዕንቁላል ብርቅ መሆናቸው ሊያቆሙ፣ ማር፣ ሥጋና ዶሮ በቅርበት የሚገኙ መሆን አለባቸው፡፡ ገበሬውም ወደ ገበያ ይዟቸው የሚቀርብ የምግብ አማራጮች መሆን ይገባቸዋል፡፡ በዚህ መንገድ በአንድ በኩል በገጠር የሚታየውን የተመጣጠነ የምግብ እጥረት መቅረፍ ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ገበሬው ለገበያ ይዞት የሚቀርበውም የምርት አማራጭ መስፋት ይኖርበታል፡፡