የብልጽግና ምስረታ፣የተቋማት ግንባታ፣ ስኬታማ ምርጫ በማካሄድ በህዝብ ዘንድ ቅቡልት ያለው መንግስት መመስረት መቻላችን፣ አረንጓዴ አሻራችንን መሬት ለማስነካት የሄድንበት ርቀት፣ ለብዝሀ ኢኮኖሚ ልማት የሰጠነው የተለየ ትኩረት፣በከተማ እና በገጠር ልናከናውናቸው የሚገቡ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎቻችን፣የኢትዮ ኤርትራ ግንኙነትና የቀጠናው ትብብር፣ ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ፣ የታላቁ ህዳሴ ግድብ አፈጻጸምና የተገኘው ስኬት፣የውስጠ ፓርቲ ስራችን አጠቃላይ ሂደት እና ውጤቱን በስፋት በመዳሰስ ጥልቀት ያለው ውይይት የተደረገ ሲሆን በጉባኤው ተሳታፊዎች በኩል ተጨማሪ ግብአት የተገኘበትና ትምህርት የተወሰደበት ነበር፡፡
ስኬቶቻችን በርካታ እና ስፋት ያላቸው ቢሆኑም ያጋጠሙን ውስጣዊ እና ውጫዊ ተግዳሮቶችም በእጅጉ የተወሳሰቡ እና ረዥም እና አድካሚ ተገዳዳሪ ሁኔታ የፈጠሩብንም ነበሩ፡፡
ከውስጣዊ ፈተናዎቻችን ስንነሳ አልጠግብ ባዩ ጁንታ በሁሉም አቅጣጫ የፈጠረብን እንቅፋት የህዝባችንን አኗኗር በእጅጉ ያወሳሰበው ከመሆኑም በላይ በአገረ መንግስቱ ቀጣይነት ላይ የህልውና ስጋት እስከመሆን የደረሰ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ህዝባችንን ዋነኛ አቅም አድርገን በመጠቀም የተቃጣብንን የህልውና አደጋ በብቃት መመከት ችለናል፡፡