የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተከትለን በሚጠበቅብን ግንባር ሁሉ ተሰልፈን መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅተናል
የጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ ጥሪን ተከትለን በሚጠበቅብን ግንባር ሁሉ ተሰልፈን መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅተናል ሲሉ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ዶክተር ቢቂላ ሁሪሳ ገለጹ፡፡
“ኢትዮጵያውያን አገራቸውን ለመታደግ የሚነሱበት ጊዜ አሁን ነው” ብለዋል፡፡
ዶክተር ቢቂላ ሁሪሳ ”ኢትዮጵያን ለማዳን አሁን የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ነን” ሲሉ ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ አኳያ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ውሳኔና ጥሪ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ከፍተኛ መነሳሳት መፍጠሩን ገልጸው፤ አርቲስቶች፣ አትሌቶች እና ሌሎች ስመ-ጥር ግለሰቦች ወደ ግንባር ለመዝመት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
“ኢትዮጵያውያን ለአገራቸው ክብር ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያውቃሉ” ያሉት ዶክተር ቢቂላ፤ መላ ኢትዮጵያውያን ያለ ልዩነት አንድ በመሆን አገራቸውን እንዲታደጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
እኛም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተከትለን በሚጠበቅብን ግንባር ሁሉ ተሰልፈን መስዋዕት ለመክፈል ተዘጋጅተናል ነው ያሉት፡፡
ወደ ግንባር ከሚዘምቱት ውጪ ያሉ ሌሎች አመራሮች ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ተግባራት እንዳይሰተጓጎሉ እንደ ወታደር 24 ሰዓት የመስራት ድርብ ኃላፊነት እንዳለባቸውም ተናግረዋል፡፡
የውጭ ኃይሎች ከውስጥ ባንዳዎች ጋር ተቀናጅተው ኢትዮጵያን ለማፍረስ እያከናወኑት ያለው ተግባር በአፍሪካ ብሎም በጥቁር ህዝቦች ላይ የተቃጣ የእጅ አዙር ቅኝ ግዛት መሆኑንም ነው የገለጹት፡፡
በመሆኑም አፍሪካውያን በፓን አፍሪካን መንፈስ ከኢትዮጵያ ጎን እንዲሰለፉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
_ አካባቢህን ጠብቅ፣
_ ወደ ግንባር ዝመት፣
_ መከላከያን ደግፍ፣