“አሸባሪው ህወሓት ለኢትዮጵያ ደህንነት አደጋ በማይሆን ደረጃ እስኪደርስ ይመታል” -ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም
አሸባሪው ህወሓት ለኢትዮጵያ ደህንነት አደጋ በማይሆንበት ደረጃ እስኪደርስ ይመታል ሲሉ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ። ጄኔራል ብርሃኑ ከኢሳት ቴሌቪዥን ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ አሸባሪው ህወሓት የአማራንና የአፋርን መሬት ይዞ እንዲኖር የሚፈልግና የሚወስን መንግሥት የለም። መከላከያ ሰራዊትም ከዚህ የተለየ አቋም የለውም።
የአማራንና የአፋርን አንዳንድ ወረዳዎችንና አንዳንድ ዞኖችን የማስለቀቅ፤ የማስለቀቅ ብቻ ሳይሆን አማራ ክልል የገባው ኃይል ሁለተኛ ወደአማራ ክልል ዝር እንዳይልና ለኢትዮጵያም ስጋት በማይሆን ደረጃ ይመታል።
ስለ አሸባሪው ህወሓት ስናስብ ከአማራ መሬት የማስወጣትን ሃሳብ አይደለም የምናስበው። ያሰመርነው መስመርም የለም። አሸባሪ ቡድኑ ለአገሪቱ ህልውና አደጋ በማይሆንበትና የውጭ ቅጥረኞች ገዝቶ ለኢትዮጵያ መፍረስ በማይሰራበት ሁኔታ መመታት አለበት።
በአገርም ላይ የህልውና አደጋ የደቀነው ወያኔ ነው እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት በትግራይ ሕዝብ ላይ የደቀነው የህልውና አደጋ የለም ያሉት ጄኔራል ብርሃኑ፤ ከትግራይ ለቅቀን ስንወጣ ያደረገውን አይተናል ብለዋል።
አሸባሪ ቡድኑ በትግራይ መብራት አጥፍቶ፣ የግንኙነት መስመሩን አቋርጦ፣ ሕዝቡ ርዳታ እንዳያገኝ ከልክሎ፣ ህጻናትን አስገድዶ በጦርነት አሰልፎ ሲያስፈጅ መቆየቱን አስታውሰዋል።