የትግራይ ሕዝብ በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደር መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው-መስከረም አበበ
ነሐሴ 12/2013 /ብልጽግና/ በኢትዮጵያ ሴቶች አደረጃጀት በአገር አቀፍ ደረጃ በወቅታዊ ጉዳይ ላይ በአዲስ አበባ በተዘጋጀው የምክክር መድረክ የትግራይ ሕዝብ በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደር መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው ያሉት የብልጽግና ፓርቲ የሴቶች ሊግ ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ መስከረም አበበ አሸባሪው የህወኃት ቡድን ከብዙሃኑ ጥቅም ይልቅ የጥቂቶችን ሃብት ሲያካብት የኖረ ድርጅት ነው ብለዋል፡፡
ኃላፊዋ አያይዘውም በመላው አገራችን የሚገኙ ሴቶች መንግስት በአሸባሪው የህወኃት ቡድን ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃ ሴቶች ደም ከመለገስ፣የድጋፍ ሰላማዊ ሰልፍ ከመውጣት ባሻገር የወር ደመወዛቸውን ከመለገስ ጀምሮ ስንቅ እስከማዘጋጀት ድረስ ድጋፍ እያደረጉ መቆየታቸውን አውስተዋል፡፡
አሸባሪው የሕወሓት ቡድን በሀገር ላይ በፈጸመው ክህደት ተጎጂ ከሆኑ አካላት መካከል በዋናነት ተጎጂዎቹ ሴቶች እና ሕፃናት ዋነኞቹ መሆናቸውን ያነሱት የውይይቱ ተሳታፊዎች ይህ የሽብር ቡድን እስኪጠፋ ለመታገል ዝግጁ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
የተዘጋጀው የውይይት መድረክ ሴቶች በሀገራቸው ጉዳይ ያላቸውን የማይናወጥ አቋም እንዲያንጸባርቁ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ የኢትዮጵያን ዕድገት የማይፈልጉ የውስጥና የውጪ ጣልቃ ሃይሎች እጃቸውን ከሀገሪቱ ላይ እንዲያነሱ ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ምቹ ሁኔታ የፈጠረ መድረክ መሆኑን ገልጸዋል።
ከመላ አገሪቱ የተወጣጡ እና ከ500 በላይ ሴቶች በተሳተፉበት በዚህ የውይይት መድረክ መንግስት የአገር ሉዓላዊነትን ከጠላት ለማስጠበቅ እያደረገ ያለውን እልህ አስጨራሽ ትግል በድል እስኪጠናቀቅ ድረስ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡