የትግራይን ህዝብ በአሸባሪው ህወሓት ከተደቀነበት አደጋ ለመታደግ የትግራይ ተወላጆች በመደራጀት እንዲታገሉ ጥሪ ቀረበ
የትግራይ ህዝብ በአሸባሪው ህወሓት ምክንያት የተደቀነበትን አደጋ ለመታደግ የትግራይ ተወላጆች በመደራጀት እንዲታገሉ ጥሪ ቀረበ፡፡ ‹‹ ራዕይ የተጋሩ ኢትዮጵያውያን ሀገር አቀፍ ህዝባዊ ንቅናቄ›› በሚል ስያሜ በትግራይ ተወላጆች ህዝባዊ ንቅናቄ ተመሰረተ፡፡
የህዝባዊ ንቅናቄ ምስረታው አስመልክቶ አቶ ሊላይ ኃይለማርያም ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት ፤ ጥቂት የሽብርተኛ ቡድኑ አባላት በትግራይ ህዝብ ላይ ያወጁትን የጥፋት ዘመቻ በተደራጀ ምልኩ መመከት ይገባል፡፡
የኢትዮጵያ ጡት ነካሽ የሆነው አሸባሪው የህወሓት ቡድን የትግራይን ህዝብ ወደ አላሰበው ጦርነት በማስገባት ከፍ ያለ ዋጋ እንዲከፍል እያደረጉት እንደሆነ ያስታወቁትአቶ ሊላይ ፣ የቡድኑን እኩይ አላማ ለማክሸፍ የትግራይ ሕዝብ በተደራጀ መልኩ ሊታገሉት ይገባል ብለዋል ፡፡
የትግራይ ህዝብ ኢትዮጵያዊ ማንነት ያለው፤ በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደርና ለኢትዮጵያ መሰረት የሆነ ሕዝብ ነው፡፡ የትግራይ ህዝብ ለዴሞክራሲ ስርዓትና አንድነትን ለማምጣት ከደርግ መንግሥት ጋር ለ17 ዓመታት እልህ አስጨራሽ ትግል ቢያካሂድም በጥቂት የአድዋ ገዥ መደቦች ትግሉ መቀማቱን ጠቁመዋል፡፡
ላለፉት 27 ዓመታት በኢትዮጵያ ህዝብ ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ መከራ ውስጥ እንዲገባ አሸባሪ ቡድኑ ትልቅ በደል መፈጸሙን ያመለከቱት አቶ ሊላይ፣ የጥፋት ቡድኑ ከማዕከላዊ መንግሥት ከሸሸ በኋላ ጥፋቱን አምኖ ህዝብን ይቅርታ ጠይቆ መቀጠል ሲገባው ህዝብ የሰጠውን እድል ረግጠው ወደ ጦርነት እንዲገባ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡