የህወሃት ቡድን ወደ ሀገር መሪነት ከመጣበት ጀምሮ እንደተከታተለ ሰው በአሁኑ ሰዓት ቡድኑ አመጾችን ወደ ቀድሞ ስልጣኑ መመለሻ መንገድ አድርጎ እየተጠቀመ ነው ሲሉ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ቲቦር ናዥ ገለጹ።
ረዳት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቲቦር ናዥ በወቅታዊ የሀገሪቱ ጉዳዮች ዙሪያ በቢቢሲ ሬድዮ አገልግሎት ላይ ቀርበው ገለጻ አድርገዋል።ቲቦር ናዥ በዚሁ ወቅት እንዳሉት መንግስት ወታደራዊ ዘመቻው መጠናቀቁን መግለጹ፤የሰብዓዊ ድጋፍ ለሚሹ ዜጎች ቶሎ ለመድረስ ጥሩ አጋጣሚ መሆኑን ገልጸዋል።
በመሆኑም የኢትዮጵያ መንግስት የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም ከአለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር እያደረገ ያለው ጥረትም አበረታች ነው።ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያን ጉዳይ እንደሚከታተሉ የጠቆሙት ቲቦር ናዥ፤የህወሃት ቡድን ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከስልጣን ለማውረድ ያለመ እንቅስቃሴ ሲያደርግ እንደነበር ለቢቢሲ ሬድዮ ተናግረዋል።
ቡድኑ ይህን አላማውን ለማሳካት ቢጥርም የሀይል ሚዛኑ ወደ መንግስት ያደላ በመሆኑ፤የሀይል መመጣጠን በሁለቱ መካከል የለም ነው ያሉት።በኢትዮጵያ የቀድሞ የአሜሪካ አምባሳደር ሆነው ያገለገሉት የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቲቦር ናዥ፤ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ የተረከቧት ኢትዮጵያ ውስጥ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እንደነበሩም ነው የጠቆሙት።