You are currently viewing ከሀገር እስከ ቂሊንጦ!

ከሀገር እስከ ቂሊንጦ!

  • Post comments:0 Comments

በሚራክል እውነቱ

አንድ የጎልማሳ ዕድሜ ያህል ሀገር ሲያስተዳድር የቆየው ጁንታው የመቀሌ ቡድን ሀገርን ለመምራት ትክክለኛ ቁመና ላይ ከመገኘት ይልቅ የከፋፋይነት ሴራውን በህዝቡ ዘንድ ሲረጭ ኖሯል፡፡ለነገሩ ቀድሞውን ቢሆን ሀገርን በብቃት ሊመራ እና ሀገራዊ አንድነትን ሊያጎለብት የሚችልበት መሰረታዊ መርህና ትክክለኛ ቁመና ላይ አልነበረም፡፡

የሀገር ጉዳይ ግድ የማይሰጠው ይህ ስግብግብ ቡድን ሀገርን ለመምራት ጦር ቢሰብቅም ይዞት የተነሳው የተደራጀ ሀገራዊ ግብ፣ራዕይም ሆነ ፕሮግራም ግን አልነበረውም፡፡ለዚህም ነው ህዝብን በፍትሃዊነት ከማስተዳደር ይልቅ ከህዝብ የሚገኘውን ሀብት ጁንታውና ቤተሰቦቹ በፍትሃዊነት ሲቀራመቱት የነበረው፤የለየለት ውንብድናና ዝርፊያ የጁንታው ቡድን መገለጫ የሆነው፡፡

ለዓመታት ሲተፋው የነበረው መርዝ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ለተፈጠሩ ሁከትና ብጥብጥ፣ስደትና ሞት ውጤት ሆነዋል፡፡ይህን ግፍ መሸከም የከበዳቸው ኢትዮጵያዊያን ዘራፊውን የመቀሌ ቡድን በህግ ለመጠየቅ የፌደራል መንግስት እያደረገ ያለውን ጥረት ከምስራቅ እስከ ምዕራብ፤ከደቡብ እስከ ሰሜን ድረስ የሚገኘው ህዝባችን አጋርነቱን በተለያዬ መንገድ አሳይቷል፡፡

መቀሌ የከተመው ይህ ዘራፊ ቡድን መጨረሻውን ያውቀዋልና ይህ ከመሆኑ በፊት ያለ የሌለ አቅሙን ተጠቅሞ ከሰራዊታችን ጋር እየተፋለ ይገኛል፤ታዲያ ምን ያደርጋል የተማመነባቸው በኮንክሪት የተሰሩ ምሽጎች ሁሉ ተደርምሰዋል ፤ታንኮችና መድፎች፣ከቀላል እስከ ካባድ መሳሪያ ያሉ ልዩ ልዩ መሳሪያዎቹም በጀግናው ሰራዊታችን እጅ ገብተዋል፡፡

ሀገርን ከማስተደደር ወደ ክልል የወረደው ይህ አምባገነን ቡድን አሁን ደግሞ በፍጥነት የመቀሌ መንግስት ብቻ ሆኖ አርፎታል፡፡ምክንያቱም ሰራዊታችን በተሰማራባቸው በሶስቱም ግንባሮች ማለትም በዛላንበሳ፣በሽሬና በራያ ግንባሮች የሚቃጣበትን ጥቃት መቋቋም የተሳነው የጁንታው ሀይሎች እያፈገፈጉ ሄደው ሄደው በጣት ቀለበት በምትገኘው መቀሌ ላይ ሊደርሱ ጥቂት ኪሎ ሜትሮች ብቻ ቀርቷቸዋል፡፡

ሀገርን ከማስተዳደር በፍጥነት ወርዶ የመቀሌ ከተማ መንግስት የሆነው ይህ ከሃዲ ቡድን ይህን እውነታ ዛሬም ድረስ መቀበል ስላልቻለ መንፈራገጡን ቀጥሎበታል፡፡በዚህ መሀል ደግሞ ተጎጂ የሆነው እጁ የሌለበት ህዝብ ነው፡፡ለነገሩ ህዝብ ለጁንታው ቡድን ምኑ ነው? ምንም፡፡

ህዝብን እያጋጨ የራሱን የፖለቲካ ስልጣን ሲያመቻች የነበረው ይህ ቡድን የመጨረሻው ሰዓት ደርሶ በህዝብ ፊት ለህግ ሊቀርብ ቀናቶች ብቻ ቀርተውታል፡፡የስልጣን ባለቤት ህዝብ መሆኑን ፣ማንም ሰው ከህግ በታች መሆኑን በተግባር ሊረዳ የጨዋታው ማጠናቀቂያ ፊሽካው ድምጽ ብቻ ቀርቷል፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ አይነኬ የሚመስለውን ይህን አምባገነን ቡድን ለህግ ቀርቦ ሲፈረድበት ለማየት ቸኩሏል፤ ህግ በተግባር ሲተረጎም ምን እንደሚመስል በቅርብ ቀን መላው ኢትዮጵያዊያን ያዩታል፡፡ ጉዞ ሀገርን ከማስተዳደር ወደ ብርቅየው ስፍራ ቂሊንጦ፡፡ጨረስኩ !

ድል ለሰራዊታችን !

ምላሽ ይስጡ