You are currently viewing ኢትዮጵያዊ እሴቶቻችን ለአብሮነታችን

ኢትዮጵያዊ እሴቶቻችን ለአብሮነታችን

  • Post comments:0 Comments

በሚራክል እውነቱ

ኢትዮጵያ የበርካታ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ብቻ ሳትሆን የተለያዩ ቋንቋዎች የሚነገርባት የቱባ ባህል ባለቤት አገር ነች። በደም ተሳስረው ለዘመናት አብረው የኖሩት የኢትዮጵያ ህዝቦች የሃይማኖት፣ የቋንቋና የባህል ልዩነቶቻቸውን አክብረው ዛሬም በፍቅርና በመከባበር ይኖራሉ። አክብረው በአንድነት ያቆዩዋቸውን እሴቶቻቸውን አጠናክሮ መቀጠልም ሰላማዊ የሆነ ማህበራዊ መስተጋብርና ጠንካራ ሀገራዊ መግባባትን እንደሚፈጥር ዕሙን ነው። ባህላዊ እሴቶች የብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ብቻ ሳይሆኑ የሀገር ሀብት እና የአንድነት መሰረታችን እንደሆኑ ከሀገር አልፎ ዓለም የሚያውቀው እውነታ ነው። ለመሆኑ እነዚህን የሀገር ሀብቶች ተፈጥሯዊ ባህሪያቸው ሳይበረዝ ለትውልድ ማስተላለፍ ቀጣይዋን ኢትዮጵያና ህዝቦቿን ለመገንባት አበርክቶው ከፍ ያለ ስለመሆኑ ምን ያህሎቻችን ተረድተነው ይሆን ? መልሱን ለእናንተ ትቼዋለሁ፡፡ እንደ መስቀል፣ ኢሬቻ፣ ኢድ አል አድሃ/አረፋ፣ አሸንዳ፣ ሻደይ፣ ሶለል፣ ጊፋታ፣ የሲዳማ ህዝብ ዓዲስ ዓመት ፊቼ ጨምበላላ፣ የጋሞ ብሄር ዘመን መለወጫ ዮ-ማስቃላና ሌሎች መሰል ሀይማኖታዊና ባህላዊ በዓላት እንደ ሀገር መከበራቸው በህዝቦች መካከል መቀራረብን ያጠናክራል፤ ማህበራዊ ትስስርና አንድነትን ይፈጥራል። እያንዳንዱ ሰው ሲከወን ያየውን ባህል የእኔ ነው የሚል ስሜት እንዲኖረው ያደርጋል።እኛ ኢትዮጵያዊያን የብዝሃ ባህል ባለቤትነታችንን አክብረን ማስከበር የምንችለው ሁሉንም በቅርበት በማወቅ እና አንዱ የሌላውን ወግ፣ባህል፣እምነትና ማህበራዊ እሴቶችን እንደራሳችን ማየትና መንከባከብ፣መጠበቅም ስንችል ነው፡፡ህብረተሰቡ ለባህላዊና ሀይማኖታዊ መገለጫዎች እኩል ዋጋና እውቅና በመስጠት መቀራረቡን ፣ፍቅሩንና አንድነቱን የበለጠ በተግባር ሊያሳይ ይገባል፤ይህ ማለት ግን ፈጽሞ የጠፋ ነው ማለት አይደለም፡፡የብልፅግና ፓርቲ እንደ ፓርቲ ትኩረት ከሚሰጣቸው እሴቶች መካከል የወንድማማችነት እሴት አንዱ ነው፡፡ ይህ እሴት ብዝሀነትን አክብራ በምትኖር እንደ ኢትዮጵያ ባለች ሀገር በእጅጉ ጠቃሚ ከመሆኑም ባሻገር በሁሉም አካባቢዎች የሚከበሩ ባህልና እሴቶችን እውቅና በመስጠት ማህበራዊ እሴቶችን ማጎልበትና የህዝቦችን ማህበራዊ መስተጋብር ማጥበቅ ይችላል። የወንድማማችነት እሴት ከሰነድ ውይይት አልፎ በተግባር እንዲተገበር ብልፅግና እንደ ፓርቲ አበክሮ ይሰራል፡፡ ምክንያቱም ወንድማማችነት መቻቻልና አንድነትን፣ፍቅርንና መተሳሰብን፣አለሁ ባይነትን የሚያጎለብት በመሆኑ ነው፡፡ ለዚህ ተፈጻሚነት ደግሞ መላው የፓርቲው አመራሮች፣አባላትና ደጋፊዎች የነቃ ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ኢትዮጵያ በርካታ ብሄር ብሄረሰቦች በጋራ የመሰረቷት ሀገር እንደመሆኗ መጠን አንዱ የሌላውን እሴትና ባህል ማወቁና ማክበሩ ጠንካራ ማህበራዊ ግንኙነትን ከመፍጠርም በላይ የምንሻትን የበለጸገች ኢትዮጵያ ለማየት ያስችለናል፡፡ ኢትዮጵያ በምትባለው ሰፊና ትልቅ ማዕቀፍ ውስጥ የሚኖር እያንዳንዱ ዜጋ የእኔ ነው የሚለው ሀገሩን ወይንም ምድሩን ብቻ ሳይሆን ህዝቡንም ጭምር ነው፤ ህዝቡ ለሚከተለው ማህበራዊ እሴቶቻችንና ባህልም ባለቤት ነው። እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ በመያዝ የጋራ እሴቶቻችንን በጋራ ማክበርና እውቅና መስጠት ሀገራዊ አንድነትን ለመገንባት እና በሰዎች መካከል ፍቅርና መተሳሰብን ለመዝራት ይረዳል ባይ ነኝ።በቅርቡ እንደ ሀገር ከሚከበሩ ሀይማኖታዊ በዓላት መካከል የመስቀል በዓልና እሬቻን መውሰድ እንችላለን፡፡እነዚህ በዓላት ለበርካታ ሺህ ዓመታት ህዝቡ በአንድነትና በፍቅር ሲያከብራቸው የኖሩ በዓላት ናቸው፡፡ህዝቡ ለቀኑ ያደረሳቸውን አምላካቸውን የሚያመሰግኑበት፣ለህዝባቸውና ለሀገራቸው ፀሎት የሚያደርጉበት፣እርስ በእርስ የሚደጋገፉበትና የሚተሳሰቡበት፣ወንድማማችነታቸውን የበለጠ በተግባር የሚያሳዩበት በዓላት ናቸው፡፡እነዚህንና መሰል በዓላት በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ በሰላም እንዲያልፉና የማንም ፖለቲካ ሀይል አጀንዳ ማስፈጸሚያ እንዳይሆኑ ደግሞ ህዝቡ በተለይ ደግሞ ወጣቶች ከጸጥታ ሀይሉ ጎን በመሆን ለሰላም ያለውን አጋርነት ሊያሳይ ይገባል እላለሁ፡፡ሰላም ለሀገራችን !ጤና ለህዝባችን !

ምላሽ ይስጡ