የአውሮፓ ፓርላማ አባላት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ያዘጋጁት ሰነድ
በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ አንድ ውሳኔ ለማሳለፍ ደፋ ቀና እያሉ የሚገኙት የአውሮፓ ፓርላማ አባላት ‘በትግራይ የሰብዓዊ ሁኔታ’ የሚል ርዕስ የያዘ የውሳኔ ሃሳብ ረቂቅ አዘጋጅው ለአባላቱ ተበትኖ ይገኛል።
ይህ ሰነድ የተለመደው በኢትዮጵያ ላይ ጫና የማሳደር ዝንባሌ በጽኑ የተንጸባረቀበት እንደሆነ ግልጽ ወጥቷል።
ጉዳዩን በቅርበት እየተከታተለ የሚገኘው ብራሰልስ የሚገኘው የቤልጂየም፣ ሉግዘምበርግና የአውሮፓ ህብረት ተቋማት የኢትዮጵያ ኤምባሲ የአውሮፓ ፓርላማ አባላት የተሳሳተ ውሳኔ ላይ እንዳይደርሱ በማስገንዘብ፤ ሰነዱ የዘነጋቸው በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ በዝርዝር ለማስረዳት ጥረት እያደረገ መሆኑ ተገልጿል።
ለፓርላማ አባላቱ ኤምባሲው በጻፈው ደብዳቤ ሰነዱ ላይ መካተት የሚገባቸው ጉዳዮች እንዳልተካተቱና የአሸባሪውን ህወሃት የግፍ ድርጊት እንዳልተመላከቱ አስገንዝቧል።
ኤምባሲው በጻፈው ደብዳቤ አሸባሪው ህወሃት በአገር መከላከያ ሰራዊት ላይ በፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት የተነሳ ግጭት መከተሉን የተዘጋጀው ረቂቅ ሰነድ እንዳላካተተው ገልጿል።
በተጨማሪም የኢትዮጵያ መንግስት የተናጠል የተኩስ አቁም ውሳኔ ቢያሳልፍም አሸባሪው ቡድን በተቃራኒው ግጭትን በማባባስ ከትግራይ ክልል ውጪ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች ወረራ መፈጸሙን ረቂቅ ሰነዱ ከግምት እንዳላስገባው አመልክቷል።
በትግራይ ክልል ያለውን የሰብዓዊ ድጋፍ ፍላጎት አጋኖ ያቀረበው ረቂቅ ሰነዱ፤ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች የደረሰውን ሰብዓዊ ቀውስ ችላ ማለቱን ኤምባሲው ማስረዳቱን ኢዜአ ዘግቧል።
ከዚህ በተጨማሪ አሸባሪው ህወሃት በአፋርና በአማራ ክልሎች ወረራ ፈጽሞ ያደረሰው የንጹሃን ግድያ፣ አስገድዶ መድፈር እንዲሁም እንስሳትን በጥይት የመግደል ግፍ በሰነዱ ሊካተት ያልቻለና ሚዛናዊነት ያልታየበት እንደሆነ ተመላክቷል።
የሰብዓዊ ድጋፍ ጥረቱን አሸባሪው ቡድን እያደናቀፈ እንደሆነ ማየት ያልወደደው ሰነዱ፤ የሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረስ ወደ ትግራይ ክልል አቅንተው የውሃ ሽታ ስለሆኑት ተሽከርካሪዎች ያነሳው ነገር የለም።
የኢትዮጵያ መንግስት በተቻለው መጠን የሰብዓዊ ድጋፍ ተደራሽ እንዲሆን ጥረት ቢያደርግም አሸባሪው ቡድን በሚፈጥረው እንቅፋት ጥረቱ በሚፈለገው ልክ ሊሆን አለመቻሉም ተጠቁሟል።
በዚህ ረገድ ውንጀላ የሚቀርበው ሰብዓዊ ድጋፍ ተደራሽ እንዲሆን ጥረት እያደረገ ባለው የኢትዮጵያ መንግስት ላይ መሆኑ የተሳሳተ ግንዛቤ በምዕራባውያኑ ዘንድ መያዙን ያሳያል።