You are currently viewing የተዘነጋው የማይካድራ አሰቃቂ ጭፍጨፋ እውነታው ሲገለጥ – ጋዜጠኛና ጸሃፊ ጀፍ ፒርስ

የተዘነጋው የማይካድራ አሰቃቂ ጭፍጨፋ እውነታው ሲገለጥ – ጋዜጠኛና ጸሃፊ ጀፍ ፒርስ

  • Post comments:0 Comments
የተዘነጋው የማይካድራ አሰቃቂ ጭፍጨፋ እውነታው ሲገለጥ – ጋዜጠኛና ጸሃፊ ጀፍ ፒርስ
ጋዜጠኛና ጸሐፊ ጄፍ ፒርስ በማይካድራ የተፈጸመውን አሰቃቂ ጭፍጨፋ እውነታውን ለማወቅ በሚል በስፍራው በመገኘት ዘገባ ሰርቷል።
ጄፍ ፒርስ በማይካድራ በንጹሃን ላይ የተፈጸመውን አሰቃቂ ጅምላ ጭፍጨፋ ታላላቆቹ የአለም የሚዲያ አውታሮች ሽፋን ሊሰጡት እንዳልፈለጉ ተናግሯል።
በማይካድራ ተጎጂዎችን በማነጋገር ባዘጋጀው ዘገባ እንደተመለከተው ሳምሪ የተባሉ የአሸባሪው ህወሓት ቡድን አባላት የአማራ ብሄረሰብ አባላትን ብቻ በመምረጥ በገጀራ በጩቤና በፋስ ተጠቅመው መጨፍጨፋቸውን ገልጿል።
አካባቢው በርካታ ሰርቶ አዳሪ ዜጎች መኖሪያ በመሆኑ ለስራ የሄዱ ወጣቶች ሰብሰብ ብለው በአንድ ቤት ማደራቸው የተለመደ መሆኑ ጉዳቱን ከፍ እንዳደረገው በምርመራው ላይ የተሳተፉ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎችን ዋቢ በማድረግ ያብራራው ጄፍ ፒርስ ፤ግድያው ከትግራይ ልዩ ሃይልና በሳምሪ ወጣቶች ቅንጅት የተፈጸመ መሆኑን አንስቷል።
በምእራባውያን የሚዲያ አውታሮች እይታ ማይካድራ ከሌሎች የኢትዮጵያ አነስተኛ ከተሞች የተለየች አለመሆኗን የሚያነሳው ጸሃፊው ጭፍጨፋውን ለደንቡ ያህል ሽፋን የሰጠው አምነስቲ ኢነተርናሽናል ብቻ እንደነበር አስረድቷል።
ድርጅቱ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ባወጣው ዘገባ ጭፍጨፋውን የእርስ በርስ ግጭት ለማድረግ ከመሞከሩም በላይ የአማራ ሃይሎችም የግጭቱ አካል ነበሩ በማለት ክስተቱን ለማቃለልና ሁለቱንም ተጎጂ ለማስመሰል ጥረት ማድረጉን በዘገባው አንስቷል።
የጭፍጨፋው ፈጻሚዎች ማንነት በተጎጂዎቹ በሚገባ ታውቀው እያለ አለማቀፉ ማህበረሰብ ምንም አለማለቱ አስገራሚ ብቻም ሳይሆን አሳዛኝ መሆኑን ይናገራል።
ጄፍ ፒርስ በሩዋንዳ የተፈጸመው አሳዛኝ ድርጊት ከአስርት አመታት በኋላ በኢትዮጵያም መከሰቱ የብዙዎችን ልብ የሰበረ መሆኑን ተናግሯል።
ከ50 እስከ 60 የሚሆኑ ሰዎች በአንድ ጉድጓድ ስለመቀበራቸው የተናገረው ጸሃፊው ጭፍጨፋው የሆነ አይነት የፖለቲካ ግብን ለማሳካት በሚል ታስቦና ታቅዶ በቅንጅት የተፈጸመና ድርጊቱም ከይቅርታ በላይ መሆኑን አስረድቷል።

ምላሽ ይስጡ